22/03/2024
የሸዋል ኢድ በዓል ፌስቲቫል!
አለም አቀፍ የማይዳሰስ ቅርስ!
ሸዋል ኢድ በሒጂራ የዘመን አቆጣጠር የረመዳን ፆም ተጠናቆ ከኢድ አልፈጥር በአል ቀጥሎ ባለው የ"ሸዋል ወር" ተከታታይ የስድስት ቀናት ፆም ከተጠናቀቀ በኋላ ለሶስት ተከታታይ ቀናት በሀረሪዎች ዘንድ ለረጅም ዘመን ሲከበር የቆየ በዓል ነው።
ይህ በዓል የባለ ብዙ ታሪክና ቅርስ ባለቤት የሆነችው ሀረር ትልቅ መገለጫና መነሻ ያላት መሆኗን ከሚያሳዩ እሴቶች መካከልም የሸዋል ኢድ በአል አንዱ ነው።
በዓሉ በሀረሪ ብሄረሰብ ዘንድ ለምዕተ አመታት ሲከበር የኖረና ባህሉንና ወጎኑ ጠብቆ ከትውልድ ትውልድ እየተወራረሰ የመጣ ባህላዊ በዓል ነው፡፡
ይህ ባህላዊ በዓል በክልሉ የመቻቻል፣ የአብሮነት እና የመረዳዳት እሴትን እንዲሁም በተለይም የቱሪዝም ዘርፉን ከማጎልበት አንፃር ጠቀሜታው የጎላ ነው።
ይህ አከባበር የወጣቶች በአልም በመባል ይታወቃል። የዚህ ምክንያትም በሀረሪዎች ወግና ስርአት መሰረት እና በሹዋሊድ እሴት መሰረት በባህላዊ አልባሳት አሸብርቀውና ወጣቶች የሚተጫጩበት በመሆኑ ነው።
የሹዋሊድ ምሽት ሀረር የምትታወቅበት የአብሮነት እሴትም ጎልቶ የሚታይበት የከተማዋ ነዋሪ የሆኑ የተለያዩ ብሔር ብሔረሰቦችም በጋራ የሚሳተፉበት ክብረ በአል ሆኗል።
በተለይም ደግሞ ወጣቶች በተዋቡ የእጅ ጥበብ ስራዎች በማራኪው የሀረሪ ባህላዊ አልባሳትና ሌሎችንም በመልበስ አምረውና ደምቀው ምሽቹንም የተዋበ የሚያደርጉበት በህብረቀለም የደመቀ አከባበር ነው።
የሸዋል ኢድ በዓል የሀገራችን አምስተኛው የማይዳሰስ ቅርስ ሆኖ በተባበሩት መንግስታት የሳይንስ፣ ትምህርት እና ባህል ድርጅት/ UNESCO በዓለም ቅርስነት መመዝገብ ችሏል