17/04/2024
ቁልፍ የፖለቲካ ስብራታችንን ከመጠገን አንጻር የብሔራዊነት ትርክት ፋይዳ ምንድነው?
እኛ ኢትዮጵያዊያን የወል ብሔረ መንግስት (Nation) በመመስረት አሰባሳቢ ሀገረ መንግስት (State) መገንባት ከጀመርንበት ጊዜ አንስቶ በርካታ ዘላቂ ወረቶች በጋራ ያካበትን ህዝቦች ነን፡፡
በጋራ ያካበትናቸው ወረቶች እንደተጠበቁ ሆነው እስካሁንም ያልተሻገርናቸው የፅንፍ አስተሳሰቦች አሉ፡፡ እነዚህ የጽንፍ አስተሳሰቦች በአንድ አመራር ትውልድ የተፈጠሩ ሳይሆን ከብሔረ- መንግስታችን ምስረታ እና ከሀገረ - መንግስታችን ግንባታ ጀምሮ የነበሩና እስካሁንም ድረስ ከእኛ ጋር ያሉ ናቸው፡፡ ዳሩ ግን እነዚህ ዋልታ ረገጥ አስተሳሰቦችና ከእነሱ የሚመነጩ ድርጊቶች የየራሳቸው ምንጮች ያላቸው ናቸው፡፡
ምንጮቻቸውም ፓርቲያችን በተለያዩ ጊዜያት በትላልቅ ሰነዶቹ ጭምር በግልፅ እንዳስቀመጣቸው ፍፁማዊ አንድነትና ፍፁማዊ ልዩነት የሚሰኙ የተቃርኖ ትርክቶች ናቸው፡፡ በብልፅግና እምነት ደግሞ ፍጹማዊ አንድነትም ሆነ ፍጹማዊ ልዩነት ሀገራችን ኢትዮጵያን የማይመስሉ ብቻ ሳይሆን የማይመጥኑም መሆናቸው ነው፡፡
እነዚህ የህዝቦች አንድነትና የሀገር ቀጣይነት ላይ ከፍተኛ አደጋ የደቀኑ ትርክቶችና ፅንፈኛ አስተሳሰቦችን ተሻግረን ሁሉም ህዝቦችና ዜጎች እኩል የሆኑበት ከተማና ሀገር እውን ለማድረግ ሁሉም ዜጋ ሃላፊነት አለበት።
የብሄራዊነት ትርክት በአንድ በኩል ሀገራችን ኢትዮጵያ ከመጣችባቸው አባጣ ጎርባጣ የሀገር ምስረታና ሀገረ መንግስት ግንባታ የሚነሱ የተቃርኖ ትርክቶችን ከስር መሰረታቸው በመግራት ሀይል ለማሰባሰብ ያግዛል፤ በሌላ በኩል ደግሞ በአርበኝነት መንፈስ የተቃኘ አንድነት፣ ወንድማማችነትና አብሮነት በመትከል የጠነከረችና ሰላማዊት የሆነች ሃገር እውን ለማድረግ ያስችለናል፡፡
ይሄን ማድረግ በመቻላችን በሃገራችን ኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን፣ እኩልነት እንዲረጋገጥ፣ ወንድማማችነት እንዲያብብ፣ የዴሞክራሲ ባህል እንዲዳብርና ሁለንተናዊ ብልጽግና እውን እንዲሆን ያስችላል፡፡