19/09/2024
ኢትዮጵያ የአፍሪካዊያን ሁለንተናዊ ተምሳሌት- በጠንካራ ቀጠናዊ ትስስር ወደ ጋራ ከፍታ!
ኢትዮጵያ የረጅም ዓመታት የሀገረ መንግስት ስርዓት ያላት፣ ቀደምት የስልጣኔ ባለቤት፣ የሰው ዘር መገኛ እንዲሁም ለአህጉር አቀፍ እና ዓለም አቀፍ ተቋማት ምስረታ የጎላ አስተዋፅኦ ያደረገች፣ ለዓለም ሰላም እና ለፍትሀዊነት አብዝታ የምትታትር ሀገር ናት፡፡
በህብር ደምቀው፣ በአብሮነት ፀንተው በመስዋዕትነታቸው ሀገራዊ ሉዓላዊነትን አስከበረው የዘለቁት ኢትዮጵያውያን ኢትዮጵያ ከእራሷ አልፋ ለአፍሪካዊያን የነፃነት ቀንድሊ ሆና ለመላው የዓለም ጥቁር ህዝብም ኩራትና ተምሳሌት እንድትሆን አስችለዋል።
ኢትዮጵያዊያን በታሪካቸው ሉዓላዊነታቸውን ያላሰደፈሩ የማንንም ያልነኩ ጨዋ፣ ታታሪና አብሮ የመኖርና ማደግ ዕሴትን ያካበቱ ጀግኖች ናቸው። የአባቶቹን ፈለግ የተከተለው ይህ ትውልድ ሀገራዊ ክብርን ያስቀደመ ወንድማማችነትና እህትማማችነትን ያማከለ አብሮ የማደግ የመደመር መርህን ይከተላል። በጀግኖች አርበኞች ደም የከበረችዋን ሀገር በላቡ በማጽናት አፍሪካዊ የብልጽግና ተምሳሌትነትን ለማረጋገጥ ይተጋል።
ዘመንን በመዋጀት ቀደምት የሆነችዋ ሀገራችን አፍሪካዊያንን በሀሳብም ሆነ በተግባር ከቅኝ ተገዥነት ይላቀቁ ዘንድ ከፓን አፍሪካኒዝም ዕሳቤ እስከ አፍሪካ ህብረት ድርጅት ምሰራታ በአንድ ተሰባስበው ለነፃነትና ሉዓላዊነታቸው እንዲታገሉ በማድረግ ከፍተኛውን ሚና ተወጥታለች፡፡
ኢትዮጵያ በወንድማማችነትና እህትማማችነት ዕሳቤ የአፍሪካዊያንንና አህጉራዊ ትስስርን በማላቅ የወል ከፍታን ለማረጋገጥ ከፍተኛ ድርሻን ተወጥታለች። ለዚህ ደሞ በየዘመናቱ የነበሩ መሪዎቿ እና በሁሉም የሀገሪቷ ጫፍ የሚገኙ ብሄር ብሔረሰቦች ሀሳብ በማመንጨትና እስከ ህይወት መስዋዓትነት በሚያስከፍል አህጉራዊ ትብብር ምስረታ ላይ እልህ አስጨራሽ ዋጋን ከፍለዋል፤ ዛሬም የኢትዮጵያ ተምሳሌትነት ዘመንን በዋጀ የትብብር መንፈስ እንደቀጠለ ይገኛል።
ይህ ትውልድ ዘመንን ይዋጃል፤ ትናንትን ከዛሬ አስተሳስሮ የነገን ይሰራል። በዚህም በመደመር መርህ ኢትዮጵያ የነበራትን ተምሳሌትነት በማላቅ ከፍ ወደአለ ሽግግር ለማድረስ በመትጋት ላይ ይገኛል። የኢኮኖሚ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ስብራቶችን በመጠገን ብልጽግናዊ የትብብር ተምሳሌትነትን ለማጽናት ዘርፈ ብዙ ተግባራትን በመከወን ላይ ነው።
የመደመር ትውልድ የአፍሪካ መዲና የሆነችዋን አዲስ አበባንም ስምና ታሪኳን በሚመጥን መልኩ ላቅ ወደ አለ ከፍታ በማሸጋገር አፍሪካዊ ተምሳሌትነቷን እያረጋገጠ ይገኛል።
ፓርቲያችን ነባር የኢትዮጵያን ሚና በማላቅ በአፍሪካ ትብብርና ፉክክር መሳለመሳ የሚጓዙበትን ጠንካራ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ትስስርን በመገንባት የህዝቦችን የቆየ ትስስር በማስቀጠል አህጉራዊ አንድነትንና ልማትን ለማዳበር እንዲሁም ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ እየተጋ ይገኛል፡፡ ሁለንተናዊ ተምሳሌትነትን በማሳለጥም በአጭር ጊዜ ከተስፋ ብርሃን ወደ የሚጨበጥ ብርሃን በመሻገር ብልጽግናዊ ተምሳሌትነትን ያፀናል።
የአፍሪካዊያን ኩራትና የነፃነት መነሻ የሆነችሁ ኢትዮጵያ ዘመንን በዋጀ የመደመር ዕሳቤ የነበራትን በማላቅ ተምሳሌትነቷን ታፀናለች። ይህ የመደመር ትውልድ የአባቶቹን አደራ የተረከበ በደም የከበረችዋን በላቡ የሚያፀና፣ ወንድማማችነትና እህትማማችነት ሰላምን፣ ብልጽግናንና የጋራ ተጠቃሚነትን መርሁ አድርጎ የሚተጋ ነው። የወል የሆነ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ትበብርን የተከተለ ቀጠናዊና አህጉራዊ ትስስርን በማጎልበትም ለጋራ ብልጽግና ይሰራል።
ሰላምንና ልማትን መነሻው ብልጽግናን መዳረሻው ያደረገው የመደመር ትውልድ ዘመኑን በሚመጥን አርበኝነት ሀገራዊ ልዕልናን ይገነባል። የመደመር ትውልድ በሉዓላዊነቱና በሀገራዊ ክብር አይደራደርም፤ የሌላን አይፈልገም፤ ለጋራ ሀገራዊና አህጉራዊ ብልጽግና በተምሳሌትነት ይተጋል፤ ቀጠናዊ ትስስርን ለጋራ ተጠቃሚነት ይገነባል።
በብልፅግና ፓርቲ የአዲስ አበባ ቅ/ፅ/ቤት