03/01/2023
+ ቁስቋም እና የተክለ ሃይማኖት ልጆች +
የግብፅዋን ቁስቋምን ለመሳለም ወደ ሥፍራው የደረስነው በሌሊት ነበር:: ይህ ሥፍራ እመቤታችን የስደትዋ መጨረሻ ያደረገችው ሥፍራ ነው:: በቦታው ጌታን ይዛ የቆየችበት ዋሻና ያስተኛችበት ሥፍራ አለ::
(ዘግይቼም ቢሆን ያየሁት ደግሞ የስደትዋ መነሻ የቤተልሔሙ ከሔሮድስ ሸሽታ ለመሔድ ስትነሣ የነበረችበት ጌታን ያጠባችበት የወተት ዋሻ በመባል የሚጠራ ሥፍራ ነው)
ቁስቋም ከቅድስት ቦታነትዋ ባሻገር በስምዋ አብያተ ክርስቲያናት በሀገራችን የታነጹባትና በዓል የሚከበርላት ሥፍራ ናት:: ደራሲው "ለምድረ ገዳምኪ ቅድስት ቁስቋም ስማ : እምፈተውኩ በጺሕየ በሰጊድ እሰዓማ (እስዕማ)" "የገዳምሽ ስምዋ ቁስቋም ትባላለች ወደ እርስዋ ብደርስ እየሰገድኩ ልስማት እመኝ ነበር" ብሎ በምኞት የተቀኘላትን ሥፍራ በኃጢአተኛ እግራችን ረግጠን መሳለም እጅግ የሚያስጨንቅ ነበር::
ገዳሙ እጅግ የሚያረጋጋ ጸጥታ ሰፍኖበታል:: ሥፍራው በረኃ ቢሆንም ገዳሙ ግን በዛፎች የተሞላ ነው:: የገዳሙ ንጽሕናና የማረፊያ ሥፍራዎቹ ጥራት አስገራሚ ነው:: ገዳሙ ከክርስቲያኖች አልፎ በገጠር መንደር ላሉ ድሆች ከከብት ልማት እርዳታ ይሠጣል::
ወደ ገዳሙ እንደገባን ሕፃን የታቀፉ እንዳብዛኛዎቹ ግብጻውያን ክርስቲያኖች ጥቁር የለበሱ ምእመናን በእልልታ ወደ ገዳሙ ሲገቡ አየን:: ልጃቸውን ክርስትና ሊያስነሡ ነው:: የሕፃኑ ልደት ቀን ብለው የሚያከብሩትም ክርስትና ያስነሡበትን ቀን ነው:: ለእልልታ አዲስ ባልሆንም እልልታቸው ትንሽ ለየት አለብኝ:: እልል ሲሉ እንደኛ ምላሳቸውን ወደ ላይና ታች በማድረግ ፈንታ ወደ ግራ ወደ ቀኝ የሚያማቱ ሲሆን እልልታው ከእልልል ወደ እሎሎሎ የቀረበ ፈጣን ነው:: በኁዋላ እንደታዘብኩት የመካከለኛው ምሥራቅ እልልታ ሁሉም "እሎልታ" ነው::
ቁስቋም ገዳምን ኢትዮጵያዊ ሆኖ መጎብኘት በጣም የሚያኮራ ነው:: በገዳሙ የኢትዮጵያዊያን መናንያን አሻራ እጅግ ጎልቶ የሚታይ ሲሆን በሥፍራው አጽማቸው ያረፈ የኢየሩሳሌም ተጉዋዥ መናንያን በዚያ በረሃ የተጋደሉ መነኮሳት በአትና ታሪክ ብዙ ነው:: የበለጠ ደስ የሚያሰኘው ግን የቁስቋምን ቤተ መቅደስ ያሠሩት ንግሥት ዘውዲቱ መሆናቸው ነው::
ወደ ቤተ መቅደሱ ዘልቀን ስንገባ በውስጡ እእንደማንኛውም የግብፅ መቅደስ ሦስት መንበርና ሦስት መቅደስ ያለው ሲሆን አንዱ የኢትዮጵያዊው ጻድቅ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት መቅደስ ነው።
ግብጻውያኑ በአንድ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በድርብ ሦስት ቅዱሳንን የሚያስቡ ከሆነ እንደ እኛ ቤተ ክርስቲያን በአንድ መንበር ሳይሆን በእያንዳንዱ ጻድቅ ስም የየራሱ መንበር ይሠራሉ። በጻድቁ የተሰየመው ታቦተ ምሥዋዕ /Alter/ ባለበት መቅደስ በር ላይ ደግሞ የጻድቁን ሥዕል በመጋረጃው ላይ ያደርጋሉ። ከቁስቋም መቅደሶች አንዱ የተክለ ሃይማኖት መቅደስም በዚህ መልኩ የተሠራ ነበር።
ተሳልመን ስንወጣ አሁን አውስትራሊያ የሚገኘው ወዳጄ ተስፉ አሰፋ ቁስቋም ከሚገኘው የጻድቁ ተክለ ሃይማኖት መቅደስ ጋር የተያያዘ አንድ ገጠመኝ ነገረኝ:: የዚህ ጽሑፍ መቋጫ ላድርገው::
ከዓመታት በፊት በታኅሣሥ ሃያ አራት የጻድቁ አባታችንን በዓል ለማክበር በግብጽ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ተሰባስበው ቁስቋም ወዳለው የጻድቁ ቤተ መቅደስ በሌሊት ይደርሳሉ። በስፍራው እንደደረሱም ከበሮ ይዘው "የኤቲሳ አንበሳ ተክልዬ ተነሣ" እያሉ እየዘመሩ በዛፎች እስከተከበበው እጅግ ሰፊው የገዳሙ ግቢ የውስጠኛ ክፍል ድረስ የጻድቁ አባታቸውን ስም እየጠሩ ገሠገሡ።
ይህንን የተመለከቱ የገዳሙ አባቶች በደስታ ተውጠው ሲመለከቱ አንድ አባት ግን እየተንሰቀሰቁ ያለቅሱ ጀመር። እኚህ አባት የተክለ ሃይማኖት መቅደስ ያለበትን ቤተ ክርስቲያን ቁልፍ የሚይዙ መነኩሴ ናቸው። የሚዘምሩትን ወጣቶች እያዩ በመደሰት ፈንታ ዕንባቸውን ለመግታት አልቻሉም። ሁኔታው ግራ ያጋባቸው ኢትዮጵያውያኑ ወጣቶች ዝማሬአቸውን ገታ አድርገው እኚህን አባት ቀርበው የለቅሶአቸውን ምክንያት ለመጠየቅ ተገደዱ።
መነኩሴውም እንዲህ ሲሉ ከዕንባ ጋር ነገሩአቸው።
"ትናንት ማታ ከሰርክ ጸሎት በኋላ እንደተለመደው ቤተ ክርስቲያኑን ልቆልፍ ስል ከተክለ ሃይማኖት መቅደስ ውስጥ ጢስ ሲወጣ ተመለከትሁ። ምናልባት የሚነድ ነገር ይኖር ይሆናል ብዬ ወደ ውስጥ ስገባ መቅደሱ በዕጣን ጢስ ተሞልቷል። ምንም የሚነድ ነገር ግን የለም። በነገሩ ተገርሜ ቤተ ክርስቲያኑን ቆልፌ ሔድኩ። ለካስ አባታችሁ እናንተ ዛሬ እንደምትመጡ አውቀው መቅደሱን አጥነው እየጠበቁአችሁ ነበር!! " አሏቸው።
የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ከመላእክት ጋር የዘመረ ቅዱስ ያሬድን ከካህናተ ሰማይ ጋር ያጠነ ተክለ ሃይማኖትን ያፈራች ቤተ ክርስቲያን ናት።
ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ታኅሣሥ 24 2008 ዓ ም